‹‹ገዥው ፓርቲም ሆነ ተቃዋሚዎች እንዲህ እናደርጋቸዋለን የሚሏቸው ነገሮች እጅግ ጠቅለል ያሉና ያልተጣሩ ናቸው›› ዶ/ር ካሣሁን ብርሃኑ፣ የፖለቲካ ሳይንስ ባለሙያ

‹‹ገዥው ፓርቲም ሆነ ተቃዋሚዎች እንዲህ እናደርጋቸዋለን የሚሏቸው ነገሮች እጅግ ጠቅለል ያሉና ያልተጣሩ ናቸው›› ዶ/ር ካሣሁን ብርሃኑ፣ የፖለቲካ ሳይንስ ባለሙያዶ/ር ካሣሁን ብርሃኑ የፖለቲካ ሳይንስ ባለሙያ ሲሆኑ፣ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉልህ ሥፍራ የሚሰጣቸው ጉዳዮች ላይ በርካታ የምርምር ሥራዎችን አሳትመዋል፡፡
ከእነዚህ ሥራዎች መካከል ትልቅ ትኩረት የሰጡት በገዥውና በተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች ባህርይ ላይ ነው፡፡ ይህን ምክንያት በማድረግ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች በምርጫ ቅስቀሳ በሚያሳዩት ባህርይ ዙሪያ ሰለሞን ጎሹ ዶ/ር ካሣሁን ብርሃኑን አነጋግሯቸዋል፡፡
ሪፖርተር፡- የምርጫ ቅስቀሳ አስፈላጊነትን እንዴት ይገልጹታል?
ዶ/ር ካሣሁን፡- ብዙ ፓርቲዎች በሕግ ተፈቅዶ በሚንቀሳቀሱበት የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ የምርጫ ቅስቀሳ አስፈላጊ ነው፡፡ ፓርቲዎች የፖለቲካ፣ የማኅበራዊና የኢኮኖሚያዊ ፕሮግራም ሊኖራቸው ይገባል፡፡ የምርጫ ቅስቀሳ ለማድረግ ሥርዓቱ የምርጫ ውድድርን የሚፈቅድ መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም የምርጫ ቅስቀሳ እንደ ኢሕአፓና መኢሶን በድብቅ የምታካሂደው አይደለም፡፡ ሕዝቡን በግልጽ ሰብስበህ ፕሮግራምህን የምታስተዋውቅበትና ከሌሎች የሚሻልበትን መንገድ የምታሳይበት ዘዴ ነው፡፡ ፓርቲው ሥልጣን ቢይዝ ከሌሎች በተሻለ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት እንደሚያሟላ፣ የአገሪቱን ጥቅም እንደሚያስጠብቅ፣ የኅብረተሰቡን ደኅንነት እንደሚጠብቅ የሚገልጽበት መሣሪያ ነው፡፡ ፓርቲዎች ፕሮግራማቸውን በየጊዜው ሊያስተዋውቁ ይችላሉ፡፡ የምርጫ ቅስቀሳ ግን በምርጫ ጊዜ ነው የሚካሄደው፡፡ በተቻለ መጠን የምርጫ ድጋፍ የሚያሰባስቡበት ነው፡፡ የምርጫ ቅስቀሳን በተሳካ ሁኔታ ለመፈጸም የገንዘብ አቅም፣ የሚዲያ ተደራሽነት፣ አመቺ ደኅንነትና ነፃነት ያስፈልጋል፡፡ የፖለቲካ ሥርዓቱ ለጤናማ የብዙኃን ፓርቲ ውድድር አመቺ ነው ወይ የሚለው በእርግጥ አጠያያቂ ነው፡፡ ለምሳሌ የሕዝብ ወይም የመንግሥት ሚዲያን በእኩልነት ባይሆን እንኳን በርትዕነት ፓርቲዎች ሊጠቀሙበት ይገባ ነበር፡፡ ፖስተር መለጠፍና መራጩን ሕዝብ ማነቃነቅና ማደራጀት የምርጫ ቅስቀሳ አካል ናቸው፡፡ ወጣቶች፣ ሴቶችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ አተኩሮ ቅስቀሳ ማድረግ ይቻላል፡፡ በእኛ አገር ሁኔታ የ1997 ዓ.ም. ምርጫ ከሌላው በጣም የተሻለ ነበር፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩና ሌሎች አመቺ ሁኔታዎች ነበሩ፡፡ በምርጫ ቅስቀሳ ረገድ ብዙ ነገሮች የተከናወኑበት ምርጫ ነበር፡፡ 
ሪፖርተር፡- በሌሎች የዳበሩ አገሮች የምርጫ መፈክር መምረጥ፣ የቅስቀሳ ስትራቴጂዎችን መቅረፅና ሊያስመርጡ የሚችሉ አጀንዳዎችን የመለየት ሥራ በጣም ወሳኝ ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች በኢትዮጵያ እንዴት ይታያሉ?
ዶ/ር ካሣሁን፡- በሌሎች የዳበሩ አገሮች ፓርቲዎች የምርጫ ስትራቴጂስቶችን ይቀጥራሉ፡፡ የሠለጠኑ፣ ከፍተኛ የሙያ ክህሎት ያላቸውና ብዙ የሚከፈላቸው ናቸው፡፡ የፓርቲው አባልም ላይሆኑ ይችላሉ፡፡ የሚዲያ ቅስቀሳን፣ ወቅትን፣ ለየትኛው የኅብረተሰብ ክፍል ምን ዓይነት አቀራረብ እንደሚያስፈልግ፣ ፖስተሮችን፣ ዓርማዎችን በተመለከተ ይወስናሉ፡፡ በእኛ አገር ሥርዓቱ ገና እየተፍጨረጨረ በመሆኑ የምርጫ ስትራቴጂን ፓርቲዎቹ አይጠቀሙም፡፡ ገዥው ፓርቲም ሆነ ተቃዋሚዎች እንዲህ እናደርጋለን የሚሏቸው ነገሮች እጅግ ጠቅለል ያሉና ያልተጣሩ ናቸው፡፡ የብዙኃን ፓርቲ ሥርዓት ከነችግሮቹ የቅርብ ጊዜ ሁኔታ በመሆኑ ይህ የማይጠበቅ ነገር አይደለም፡፡ ለምሳሌ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራሞች ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ ናቸው፡፡ ሌሎች የምርጫ ቅስቀሳ ፕሮግራሞችም እንዲሁ ወጪያቸው ቀላል አይደለም፡፡ በዳበሩ አገሮች ለሚዲያ የሚከፈለው ገንዘብ እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በሥልጣን ላይ ያለ ፓርቲና መሪም ቢሆን የመንግሥትን በጀት መጠቀም ስለማይችሉ ወጪውን ለመሸፈን ይቸገራሉ፡፡ በእኛ አገር መንግሥትና ፓርቲ ስለተቀላቀሉ አስቸጋሪ ነው፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዳቅማቸው አንዳንድ ነገር ይሞክራሉ፡፡ በተለይ ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራን ለመሥራት፣ ወኪሎቻቸውን ወደ ምርጫ ክልሎች በመላክ ድጋፍ ለማሰባሰብ ይሞክራሉ፡፡ የገዥው ፓርቲ እንቅስቃሴ ሻል ያለ ነው፡፡ በራሱ በፓርቲውም፣ የመንግሥትን ሥልጣን በመጠቀምም የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል፡፡  

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር